Saturday, September 10, 2011

‹‹ልትሾም ነው››


http://www.ethiopianreporter.com/editorial/294-editorial/2746-2011-07-23-07-38-18.html
‹‹ልትሾም ነው
‹‹ከዕለታት አንድ ቀን አንድ ሰው በውድቅት ሌሊት አፍላ እንቅልፍ ጭልጥ አድርጎ ወስዶት ሳለ አሰቃቂ ሕልም ያያል፡፡
››
ሕልም አላሚው በሁኔታው ተደናግጦ አይ ዘንድሮስ መሞቴ ነው መሰል አለ፡፡

በዚህም ምክንያት የመንፈስ መረጋጋት ስላጣ ባቅራቢያው ወደሚገኝ ሕልም ተርጓሚ ካህን ሔደና ‹ዛሬ አሰቃቂ ሕልም አየሁ፣ መሞቴ ነው መሰለኝ› አለው፡፡

‹ሕልምህ ምንድን ነው? እስቲ ንገረኝ አለው› ሕልም ተርጓሚው ካህን፤
‹በውድቅት ሌሊት አፍላ እንቅልፍ ጭልጥ አድርጎ ወስዶኝ ሳለ፣ እጅ እግሬ ሽባ ሆኖ፣ ዓይኔ ታውሮ፣ ጆሮዬ ደንቁሮ አየሁ፡፡ ብንን ብል ሕልም ሆነ› አለው፡፡

‹አትሞትም አይዞህ፣ አትሞትም፣ ልትሾም ነው› አለው ተርጓሚው ካህን፡፡

‹እንዴት ልትሾም ነው?› አለና የሕይወት ሞት ሞተ ሕልመኛው፡፡ ሕልም ተርጓሚው እንደተገለጠለት ሕልሙን ይተረጉምለታል፡፡

‹ስማ! እጅ እግርህ ሽባ ሆኖ ማየትህ፣ ዱሮ ወዲህና ወዲያ እየተሯሯጥክ ላገርህ፣ ለወገንህ፣ ለራስህ የሚጠቅም ሥራ ትሠራ ነበር፡፡ ከተሾምህ ግን ይህ የትሩፋት ሥራ የለም፡፡ ሹም ነህ ተብለህ፣ እጅ እግርህን ኮርትመህ መቀመጥህ እኮ ነው፡፡ ዓይንህን ታውሮ ያየኸውማ ላገር፣ ለሕዝብ፣ ለወገን ጉዳይ ሰው ሊያነጋግርህ በግር በፈረስ ሲፈልግህ ይህን ጋጋታ ማየት አትፈልግም፡፡ ከበር የሚቆመው አጋፋሪህ ከእንግዳ ጋር ናቸው፤ ሥራ ይበዛባቸዋል፤ ወደ ውጭ ሊሔዱ ነው፤ ከዚህ ወግድ እያለ ፈላጊህን ሁሉ ያባርረዋል፡፡ ስለዚህ ዓይንህ ከሌላው ሰው ይሰወራል ይጨፈናል፡፡

‹ጆሮህ መደንቆሩ ደግሞ ድሀው ሕዝብ፣ ሥራ አጡ፣ በሽተኛው፣ አቤት ባዩ፣ መንገደኛው፣ ፍርድ የጐደለበት፣ ግፍ የተሞላበትም ሁሉ ዋይ ዋይ፣ አቤት አቤት፣ ሲል የድሀውን ዋይታ፣ የድሀውን አቤቱታ አትሰማም› አለውና አጠቃልሎ አስረዳው፡፡››

ይህ ከፍ ብለን የጠቀስነው ሕልምና ፍቺ ከሦስት አሰርት ዓመታት በፊት የተጻፈና በመጽሐፍም የታተመ ነው፡፡ ሕልም ተርጓሚው ካህን እንዳለው በሕዝብ ላይ መሾም ሕዝብን ለማገልገል እንጂ፣ በሕዝብ ላይ ለመገልገል መሆን የለበትም የሚለው መልዕክት ዛሬም እውንም፣ አንገብጋቢም በመሆኑ ግን ልንጠቀምበት ተገደናል፡፡

ሁሉም ሹመኛ በሕዝብ እየተገለገለ አይደለም፡፡ ሕዝብን ለማገልገል የሚፈልጉና የሚንቀሳቀሱም አሉ፡፡ አሌ የማይባለው ግን በሕዝብ መገልገል የሚፈልጉ ሹመኞች እየተበራከቱ መምጣታቸው ነው፡፡

‹‹ልትሾም ነው›› የሚለው አባባል፣ ሕዝብን ለማገልገል ኃላፊነት ልትወስድ ነው መሆኑ ቀርቶ፣ ‹‹ልትገለገል ነው››፣ ‹‹ልትጠቀም ነው›› ሆኖ እየመጣ ነው፡፡

በአሁኑ ጊዜ በኅብረተሰቡ ብዙና የተለያየ አቤቱታና ቅሬታ አለ፡፡ መንግሥት ለምን ይህን ያደርጋል? ለምን እንደዚህ ዓይነት መመርያ ያወጣል? ወዘተ. የሚል፡፡ እነዚህን አቤቱታዎችና ቅሬታዎችን ተንቀሳቅሶ የሚከታተል አካል፣ የሚያይ ዓይንና የሚያዳምጥ ጆሮ ቢያገኙ ኖሮ በቀላሉ የሚፈቱና ከመግባባት ላይ የሚደርሱ ናቸው፡፡ የሚንቀሳቀስ እግር፣ የሚያይ ዓይንና የሚያዳምጥ ጆሮ ስላጡ ግን ቅሬታዎችና አቤቱታዎች ሊወገዱ አልቻሉም፡፡

በአከራይ ገቢ ላይ ታክስ ተጨምሯል ብሎ ቤት አከራይ እያማረረ ነው፡፡ በቃል እንጂ በመመርያም አይደለም የሚል አቤቱታም አለ፡፡ አስፈላጊ ነው ብሎ መንግሥት ካመነበት በመመርያ ወይም በአዋጅ አውጥቶ ከአከራይም ጋር ተወያይቶና አሳምኖ ማድረግ ይችላል፡፡ የጽሑፍ መመርያ ወይም ሕግም ስለሌለ፣ የሚያስረዳም ስለሌለ ግን ቅሬታ ይሰማል፡፡

ግብር ጨምሩ ተብለናል ብለው ቅሬታ የሚያሰሙ ባለጥቃቅን ንግዶች በርካታ ናቸው፡፡ ሁለት ሺሕ እንከፍል የነበረ ሃያ ሺሕ ክፈሉ ተባልን እያሉም አቤት እያሉ ናቸው፡፡ የሚያስረዳና የሚያወያይ ስለሌለ ቅሬታ አለ፡፡ ቀረብ ብሎ የሚያዳምጥ፣ ቀረብ ብሎ የሚያይ፣ እየተንቀሳቀሰም ችግሩን የሚያጠናና አወያይቶ የሚያሳምን ካለ በቀላሉ የሚፈታ ነበር፡፡

የንግድ ፈቃድ አሳድስ የሚለውም ብዙ መንከራተት እያስከተለ ነው፡፡ ውል ክፍል መሔድ፣ ባንክ መሔድ፣ ውጭ የነበረ ሰው እባክህ ተመለስና ጨርስ ብሎ መለመን ወዘተ.፡፡ ለምን ይታደስ ተባለ አንልም፡፡ ምክንያት ይኖራል፤ በተጨማሪም ግልጽና ሕጋዊ የሆነ ፈቃዶች እንዲኖሩ ማድረግ ተገቢ ነው፡፡ ነገር ግን አንዱ እስከ ሐምሌ 30 ይላል፤ ሌላው እስከ ሐምሌ 15 ይላል፤ ሌላው የብቃት ማረጋገጫ አምጡ ይላል፤ ሌላው ይታሸጋል ይላል፤ ሌላው ሰባት ዓመት ያሳስራል የሚል ወረቀት ይጽፋል፡፡ ውጥንቅጡ ይወጣል፡፡ ቀላሉ ይካበዳል፤ በመግባባት የሚፈታውን ቅሬታ ያወሳስበዋል፡፡

ለምን ታክስ ተጨመረ አይባልም፤ ምክንያት ሊኖረው ይችላል፡፡ ለምን ታክስ ክፈሉ አይባልም፤ ታክስ የግድ መክፈል አለበትና፡፡ ለምን ፈቃድ ይታደስ ተባለ አይባልም፤ መታደስ አለበትና፡፡

ችግሩ ያለው ተደራርቦ ሲመጣ፣ ማስፈራት ሲታከልበት፣ አለበለዚያ ሲበዛበት ያ በቀና መንፈስ ሲሠራ የነበረም ምን እየሆነ ነው ብሎ መደናገርና መረበሽ ይፈጠርበታል፡፡

መረጋጋት በንግድ ዓለም አስፈላጊ ነው፡፡ መንግሥት ያዳምጥ፤ እየተንቀሳቀሰ ያጥናና ያረጋግጥ፤ ችግሩንም ይመልከት፤ እየተወያየም መፍትሔ ያስቀምጥ፤ ያኔ ሁሉም ነገር ቀላል ይሆናል፡፡

ዋናው ቁም ነገሩ ከታች እስከላይ ያለ ሹመኛ እግሬም፣ ዓይኔም፣ ጆሮዬም ሕዝብን ለማገልገል እንጂ ሕዝቡ እንዲያገለግለኝ አልጠቀምበትም ብሎ ማረጋገጥ አለበት፡፡  
ምንጨ ።http://www.blogger.com/post-edit.g?blogID=6975122765494067198&postID=4365213638690244223

በርካታና ትላልቅ የልማት፣ የፍትሕ፣ የዴሞክራሲም አጀንዳዎች ስላለን በጥቃቅን ቅሬታዎች አናደብዝዛቸው፤ እንቀራረብ፤ እንተያይ፤ እንደማመጥ፤ እንመካከር፡፡
አሁኑኑ!!

No comments:

Post a Comment