Saturday, August 11, 2012

የውጤት ትንተናና ማብራሪያ በ ሐሰን መሐመድ ሐሰን


ምዕራፍ አራት፡- የውጤት ትንተናና ማብራሪያ
ጥናቱ ዓላማ አድርጐ የተነሳው በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትናአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ያለውን ተዛምዶ ለመመርመር ነው፡፡ ለዚህም እንዲረዳ በመጠይቅ አማካኝነት የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት፣ በአንብቦ የመረዳት ፈተና ደግሞ የተማሪዎችአንብቦ መረዳት ችሎታ ውጤት በመረጃነት ተሰብስቧል፡፡ ስለዚህ የጥናቱ ትኩረት የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶ በመፈተሽ የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከት አቅጣጫ ለማመልከት ነው፡፡ በዚህ ላይ የተመሰረቱት የጥናቱ ውጤት ትንተናና የውጤቱ ማብራሪያ በቅደም ተከተል እንደሚከተለው ቀርበዋል::
4.1.የውጤት ትንተና  
የጥናቱ የመጀመሪያው መሪ ጥያቄ "በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ተዛምዶ አለ?" የሚል ነው፡፡ ይህንን ጥያቄ ለመመለስ የተማሪዎቹ የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶ በፒርሰን የተዛምዶ መወሰኛ ቀመር ተሰልቷል፡፡ ውጤቱም ቀጥሎ በሰንጠረዥ 1 ተመልክቷል፡፡
ሠንጠረዥ 1፣የማንበብ አመለለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶ በፒርሰን የተዛምዶ መወሰኛ ቀመር፡፡
ተላውጦ
የናሙና ብዛት
አማካይ ውጤት
መደበኛ   ልይይት
ተዛምዶ
1
2
1.  የማንበብ አመለካከት
2.  የአንብቦ መረዳት ችሎታ 
270
85.49
59.30
11.86
14.50
1.00
0.053*

1.00
                                  የጉልሕነት ደረጃ P>0.05*
በሠንጠረዥ 1 ላይ ለማየት እንደሚቻለው የተማሪዎቹ የማንበብ አመለካከት አማካይ ውጤት ከሚጠበቀው ውጤት (72) ከፍ ያለ (85.49) ሆኖ ተገኝቷል፡፡ የአንብቦ መረዳት ችሎታቸውም ከሚጠበቀው አማካይ ውጤት (50) በላይ (59.30) ሆኖ ተመዝግቧል፡፡ ነገር ግን በማንበብ አመለካከትና በአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል የታየው ተዛምዶ (r=0.053,P>0.05) ቢሆንም ጉልህ ግን አይደለም፡፡ በተላውጦዎቹ መካከል የታየው የተዛምዶ መጠን የጋራ ባሕሪ በመቶኛ ሲሰላ ከአንድ በታች (0.28%) ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ከዚህ በመነሳት በሁለቱ ተላውጦዎች መካከል ያለው ተዛምዶ በጣም ዝቅተኛ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ ይህም የማንበብ አመለካከት መኖር ወይም አለመኖር ከአንብቦ መረዳት ችሎታ ጋር የሚያገናኘው ነገር የለም፤ ቢኖርም በጣም አነስተኛ ነው ለማለት የሚያስችል ይመስላል፡፡
በመቀጠልም የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታቸውን የመተንበይ ጉልህ ድርሻ ይኖረው ወይም አይኖረው እንደሆን ለመለየት ትንተና ተደርጓል፡፡ ለዚህም የጥናቱ መሠረታዊ ጥያቄ "የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታቸውን የመተንበይ ድርሻው ምን ያህል ነው?" የሚል ሲሆን፣ ይህንን ጥያቄ ለመመለስ የቀላል ድኅረት ትንተና (Simple Regression) ተደርጓል፡፡ ውጤቱም በሰንጠረዥ 2 ላይ እንደሚከተለው ተመልክቷል፡፡
ሠንጠረዥ 2፣ የማንበብ አመለካከት አንብቦ የመረዳት ችሎታን የመተንበይ ድርሻ በቀላል ድኅረት ትንተና (Simple Regression)

ተላውጦ
የተጋርቶ መጠን
ድኅረታዊ መጣኝ
Coefficient
መደበኛ ድኀረታዊ መጣኝ
Beta (β)
የቲ- ዋጋ
T- Statstics
የስሕተት ይሁንታ
Significance
የማንበብ አመለካከት
0.003
0.065
0.053
0.873
0.383
ጥገኛ ተላጦ = የአንብቦ መረዳት ችሎታ ውጤት
የሠንጠረዥ 2 የቀላል ድኅረት ትንተና (Simple Regression) ውጤት እንደሚያመለክተው የማንበብ አመለካከት በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ላይ ያለው ድርሻ (R² = 0.003፣ F=0.762፣ P>0.05) ጉልህ ሆኖ አልተገኘም፡፡ ይህም ተላውጦው በተማሪዎች የአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ጉልህ ድርሻ ወይም አስተዋፅኦ እንደሌለው ያመለክታል፡፡ ወይም ደግሞ የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት መኖር ወይም አለመኖር በአንብቦ መረዳት ውጤታቸው ላይ የሚያመጣው ተፅዕኖ አይኖርም ማለት ነው፡፡
ተላውጦው በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ላይ ያለው ቀጥተኛ ተፅዕኖ ወይም ድርሻ ምን ያህል እንደሆነ ለማወቅ በመደበኛ ድህረታዊ መጣኝ (Beta Coefficient) ተሰልቷል፡፡ በዚሁ መሰረት የማንበብ አመለካከት በአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ያለው ተፅዕኖ (β = 0.053፣ t = 0.873፣ P>0.05) ሲሆን፣ ይህም የማንበብ አመለካከት በአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ጉልህ ድርሻ እንደሌለው ያመለክታል፡፡ ከዚህም በመነሳት የማንበብ አመለካከት በአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ በጣም አነስተኛ ነው ወይም ጭራሹኑ የለም ለማለት ይቻላል፡፡
ከሠንጠረዥ 2 ለመረዳት እንደሚቻለው በዚህ የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት ድርሻ በአንብቦ መረዳት ላይ የተጋርቶ መጠን መለኪያ (Coefficient of Detrmination) R²=0.003 ነው፡፡ ከዚህ በመነሳት የማንበብ አመለካከት ከአንብቦ መረዳት ችሎታ ጋር 0.3% የልይይት መጠን ይጋራሉ ወይም የማንበብ አመለካከት በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ውጤት ላይ በዚህ ልክ ተፅዕኖ አሳድሯል ለማለት ይቻላል፡፡
የዚህ ጥናት ሶስተኛ መሠረታዊ ጥያቄ "በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ያለው ተዛምዶ በፆታ ልዩነት ያሳያል?" የሚል ሲሆን፣ ይህንን ለመመለስ ባለሁለት ናሙና ቲ-ቴስት ተግባራዊ ሆኗል፡፡ ውጤቱም እንደሚከተለው በሰንጠረዥ 3 ቀርቧል፡፡
ሠንጠረዥ 3፣ የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ በፆታ (በባለሁለት ናሙና ቲ-ቴስት)

ተላውጦ

ፆታ
የተሳታፊ ብዛት
270
አማካይ ውጤት
መደበኛ ልይይት
(SD)
የነፃነት ደረጃ
(df)
የቲ-ዋጋ
(t-test)
የይሁንታ
ስህተት
(Sig.)
የማንበብ አመለካከት

ወንድ

129
84.75
12.32



268


-1.011
0.313
አንብቦ መረዳት
58.84
14.48
- 0.496
0.620
የማንበብ አመለካከት

ሴት

141
86.22
11.50
-1.011
0.313
አንብቦ መረዳት
59.72
14.62
-0.496
0.620
ሰንጠረዥ 3 እንደሚያመለክተው የወንድ ተማሪዎች የማንበብ አመለካከት አማካይ ውጤት (84.75) ከሴቶቹ አማካይ የማንበብ አመለካከት ውጤት (86.22) ያነሰ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ በሌላ በኩል ደግሞ የወንዶች መደበኛ ልይይት (12.32) ከሴቶች መደበኛ ልይይት (14.48) ዝቅ ያለ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ይህም ሴት ተማሪዎች ከወንድ ተማሪዎች የተሻለ የማንበብ አመለካከት ቢያሳዩም (t = -1.011፣ df = 268፣ P=0.313) ልዩነቱ የቲ-ዋጋ ግን ጉልህ ባለመሆኑ ልዩነት አላቸው ለማለት አያስደፍርም፡፡
በተጨማሪም የተማሪዎቹን የአንብቦ መረዳት ችሎታ (ከሰንጠረዥ 3 ለመገንዘብ እንደሚቻለው) የወንድ ተማሪዎች አንብቦ የመረዳት ችሎታ አማካይ ውጤት ከሴቶቹ ዝቅ ብሎ (58.84) የተገኘ ሲሆን፣ የሴቶቹ ተማሪዎች የአንብቦ መረዳት ችሎታ ከወንዶቹ በልጦ (59.72) ተገኝቷል፡፡ መደበኛ የልይይት መጠናቸው የወንዶቹ (11.50) ሲሆን፣ የሴቶቹ ደግሞ (14.62) መሆኑን ያመለክታል፡፡ ይህም በአንብቦ መረዳት ችሎታ ከወንዶቹ ይልቅ ሴቶቹ ተማሪዎች (t= -0.496 df = 268፣ P= 0.620) የተሻለ ልዩት እንዳላቸው ቢያመለክትም ልዩነቱ የቲ-ዋጋ ጉልህ ባለመሆኑ የጎላ ልዩነት አላቸው ለማለት አያስችልም፡፡
በአጠቃላይ የውጤት ትንተናው እንዳመለከተው የጥናቱን ዓላማ ከግቡ ለማድረስ  በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና አንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ያለውን ተዛምዶ ለመመርመር ተችሏል፡፡ በጥናቱ ለተነሱት ሶስት ጥያቄዎችም መልስ ተገኝቷል፡፡ በዚህም በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ተዛምዶ የለም፡፡ የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታቸውን የመተንበይ ድርሻ የለውም፡፡ እንዲሁም በማንበብ አመለካከትና በአንብቦ መረዳት ችሎታ ከወንድ ተማሪዎች ይልቅ ሴት ተማሪዎች የተሻሉ ቢሆንም ልዩነቱ ጉልህ አለመሆኑ በስታስቲክስ ተገልጧል፡፡
  4.2. የውጤት ማብራሪያ
የዚህ ጥናት ትኩረት በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ መካከል ያለውን ተዛምዶ ይመለከታል፡፡ ስለዚህም በመጠይቅና በፈተና በተሰበሰቡ መረጃዎች አማካኝነት የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት አንብቦ ከመረዳት ችሎታቸው ጋር ያላቸው ተዛምዶ በንፅፅር ታይቷል፡፡ የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታን የመተንበይ ጉልህ ድርሻ በፆታ ልዩነት ያሳይ ወይም አያሳይ እንደሆን ለመፈተሽ በተለያዩ ገላጭና ተንባይ ስታትስቲክሶች ተተንትኗል፡፡
በሰንጠረዥ 1 ላይ እንደሚታየው ይህ የተማሪዎቹ አማካይ የማንበብ አመለካከት አማካይ ውጤት መጠን (85.49) ከአንበቦ መረዳት ውጤታቸው አማካይ ውጤት (59.30) አንፃር ሲታይ (r=0.053፣ P>0.05) ተለዋዋጮቹ የሚጋሩት የጋራ ባሕሪ (0.28%) በጣም ዝቅተኛ በመሆኑ በማንበብ አመለካከትና በአንብቦ መረዳት መካከል ተዛምዶ አልታየም፡፡ ከዚህ በመነሳት ተማሪዎቹ ከፍተኛ የሆነ የማንበብ አመለካከት ቢኖራቸውም የአንብቦ መረዳት ችሎታቸው ግን አነስተኛ ነው ለማለት ይቻላል፡፡ ተማሪዎቹ ከፍተኛ የሆነ የማንበብ አመለካከት እያላቸው በአንብቦ መረዳት ችሎታቸው ዝቅተኛ ውጤት ያስመዘገቡበት ምክንያት ምናልባት ተማሪዎቹ የቀረበላቸውን ንባብ በግልፅና በትክክል አለመረዳት ሊሆን ይችላል፡፡ በተጨማሪም ተማሪዎቹ የንባቡን ይዘት፣ መዋቅርና ቴክስት የመተቸት ብቃታቸው አናሳ በመሆኑ ሳይሆን አይቀርም፡፡ ይህም ምክንያት  በሳላበስ (2008)፣ በፒትስቸር (2010) በናንሲ (1989) ጥናት ከተገለጠው ሐሳብ ጋር የሚስማማ ይመስላል፡፡ በሌላ በኩል ግን የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት ከአንብቦ የመረዳት ችሎታ ጋር ተዛምዶ አለመኖር አቡ-ራቢያ (1996) የቴክስቱ ይዘት ሳይሆን የቴክስቱ ቋንቋ አንብቦ ለመረዳት ተፅዕኖ አሳድሯል ግሪአኒ (1987) የመኖሪያ አካባቢና የማንበቢያ ትርፍ ጊዜ ተዛምዶ አላቸው፤  ቡክሆረስት-ሄንግና ፔሪራ (2008) ትርፍ ጊዜን በንባብ ተግባር ላይ አለማዋል በማንበብ አመለካከት ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል በሚል ከደረሱበት ድምዳሜ ጋር ተደጋጋፊ አይደለም፡፡ በተጨማሪም የምርምሮቹ ውጤቶች ያልተደጋገፉበት ምክንያት ምርምሮቹ የተካሄዱት በተለያዩ አካባቢዎችና የተለያዩ ባሕላዊ ዳራ ባላቸው ተማሪዎች በመሆኑ ሊሆን እንደሚችል መገመት ይቻላል፡፡
በትንተናው ለማሳየት እንደተሞከረው ጥናቱ ትኩረት ያደረገበት ሌላው ጉዳይ የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታን  በመተንበይ ረገድ የሚኖረውን ጉልህ ድርሻ ይመለከታል፡፡ በሰንጠረዥ 2 ላይ እንደተመለከተው  የማንበብ አመለካከት በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ላይ ያለው ድርሻ (R² = 0.003፣ F = 0.762፣ P>0.05) ሲሆን፣ ይህም ተለዋዋጩ በተማሪዎች የአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ጉልህ ድርሻ ወይም አስተዋፅኦ እንደሌለው ያመለክታል፡፡ ከዚህ ባሻገር የማንበብ አመለካከት በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ላይ ያለው ድርሻ (β = 0.053፣ t = 0.873፣ P>0.05) ሲሆን፣ ይህም የማንበብ አመለካከት አንብቦ የመረዳት ችሎታ ድርሻ እንደሌለው ያመለክታል፡፡ በተጨማሪም በማንበብ አመለካከትነ አንብቦ የመረዳት ችሎታ የተጋርቶ መጠን መለኪያ R² (Coefficient of Detrmination) R² = 0.003 ወይም 0.3% ሆኖ ተገኝቷል፡፡ ከዚህ በመነሳት የማንበብ አመለካከት ከአንብቦ የመረዳት ችሎታ ጋር 0.3% የልይይት መጠን ይጋራሉ ወይም በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ላይ በዚህ ልክ ተፅዕኖ አሳድሯል ለማለት ይቻላል፡፡ ከጥናቱ ውጤት ለመረዳት እንደሚቻለው የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታን ለመተንበይ ያልቻለበት ምክንያት ተለዋዋጮቹ ተዛምዶ ስለሌላቸው ሊሆን ይችላል ብሎ መገመት ይቻላል፡፡ የዚህ ጥናት ውጤት የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታን የመተበይ ጉልህ ድርሻ አለው ከሚለው ከዴይና ባምፎርድ (1982) ከኮንሊ (1992) ከአሌክሳንደርና ፊለር (1992) ከሮኢና ስሚዝ (2005) የምርምር ግኝቶች ጋር ሲቃረን፤ የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታን የመተንበይ ድርሻው የጎላ አይደለም ከሚሉት ከራንስበሪ (1973) ከሒዚግነቶንና አሌክሳንደር (1984) ከማና እና ማይሽፍ (1987) ከሞሪሰን፣ ጃኮብስና ስዊንያርድ (1999) ከአፕሊጌትና አፕሊጌት (2004) ከስችማይት (2009) የምርምር ግኝቶች ጋር ተደጋገፊነት አሳይቷል፡፡
በሠንጠረዥ 3 ላይ እንደተመለከተው የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ በፆታ ልዩነት እንዳለውና እንደሌለው የተደረገው የጥናት ውጤት ትንተና  እንዳመለከተው በማንበብ አመለካከት ሴት ተማሪዎች ከወንድ ተማሪዎች የተሻለ አመለካከት ቢታይባቸውም የቲ- ዋጋ ግን ጉልህ ሆኖ አልተገኘም፡፡ በተመሳሳይም የሴት ተማሪዎች አንብቦ መረዳት ችሎታ ከወንድ አቻዎቻቸው በልጠው ቢገኙም የቲ- ዋጋ ልዩነቱ ጉልህ እንዳልሆነ ያመለክታል፡፡ በመጠይቅና በፈተና የተገኘው የጥናት ውጤት ከሊናና ካሪም (2007)፣ ከክሪስቲናና ጆናታን (2011)፣ ከዊዊ (2009)፣ ጥናት ጋር ሲደጋገፍ፤ ከናንሲ (1989) ጥናት ጋር በከፊል ይስማማል፡፡  ነገር ግን የጥናቱ ውጤት ከሳላበስ (2008)፣ ከባስ (2012)ና ከተራቪስ (2010)፣ የጥናት ውጤት ጋር አይደጋገፍም፡፡
ከጥናቱ ውጤትና ከክለሳ ድርሳን የተገኙት መረጃዎች እንደሚጠቁሙት የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ እንዳይጎለብት የሚያደርጉት ምክንያቶች አዎንታዊ የማንበብ አመለካከት እንዲዳብር ትኩረት ባለመሰጠቱ፣ መምህራን የበርካታ ተማሪዎቻቸውን የማንበብ አመለካከት ዝንባሌ ግምት ውስጥ ሳያስገቡ የዕለት ተዕለት ተግባራቸውን ማከናዎናቸው እንዲሁም ወላጆች ማንበብን የትርፍ ጊዜ ተግባር አድርገው መቁጠራቸው ናቸው፡፡
በአጠቃላይ ከጥናቱ ውጤት ለመረዳት እንደሚቻለው የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ ተዛምዶ የላቸውም፡፡ የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት አንብቦ የመረዳት ችሎታቸውን የመተንበይ ጉልህ ድርሻ የለውም፡፡ በማንበብ አመለካከት ሴት ተማሪዎች ከወንድ ተማሪዎች የተሻለ አመለካከት ታይቶባቸዋል፡፡ ልዩነቱ ጉልህ ባይሆንም የሴት ተማሪዎች አንብቦ የመረዳት ችሎታ ከወንድ አቻዎቻቸው ጋር ሲነፃፀር ብልጫ አለው፡፡ በአሌክሳንደርና ፊለር (1976)፣ ዊየርና ዊየር (1994)፣ በብሮምፊ (2004)፣ በማክኪና፣ ኪአርና ኢልስዋርዝ (1995)፣ በራሲኒስኪና ፓዳክ (2000) እንደተጠቆመው ለነዚህ የጥናት ውጤቶች ግኝት እንደ አሉታዊ ምክንያት የሚጠቀሱት የተማሪዎች የማንበብ አመለካከቶች ብቻ ሳይሆኑ መምህራን በትምህርት ቤት፣ ወላጆች በመኖሪያ ቤት እንዲሁም በአካባቢያቸው በማንበብ አመለካከታቸው ላይ ተፅዕኖ ስለሚያደርሱባቸው ሊሆን ይችላል፡፡










ምዕራፍ አምስት፡- ማጠቃለያ፣ መደምደሚያና መፍትሔ
የጥናቱ መግቢያ፣ ከጥናቱ ጋር ተዛማጅነት ያላቸው ክለሳ ድርሳናት፣ የአጠናን ዘዴና የጥናቱ ውጤት ትንተናና ማብራሪያ በቅደም ተከተላቸው መሠረት ያለፉት ምዕራፎች የትኩረት ነጥቦች ነበሩ፡፡ በዚህ ምዕራፍ ደግሞ ማጠቃለያ፣ መደምደሚያና የመፍትሔ ሐሳቦች ይቀርባሉ፡፡
5.1. ማጠቃለያ
የጥናቱ ዋና ዓላማ የተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶን መመርመር መሆኑ በቀዳሚዎቹ ምዕራፎች ተገልጧል፡፡ በዚህም መሠረት በጥናቱ መልስ እንዲገኝባቸው የተነሱት መሠረታዊ ጥያቄዎች የሚከተሉት ነበሩ፡፡ በፋሲሎ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የሚማሩ የ10ኛ ክፍል ተማሪዎች፡-
1.  በማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ተዛምዶ አለ?
2.  የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታቸውን የመተንበይ ድርሻው ምን ያህል ነው?
3.  በማንበብ አመለካከትና በአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ያለው ተዛምዶ በፆታ ልዩነት ያሳያል? የሚሉ ናቸው፡፡
ከላይ የቀረቡትን መሠረታዊ ጥያቄዎች በአስተማማኝነት ምላሽ ለመስጠት እንዲቻልም መጠይቅና ፈተና በመረጃ መሰብሰቢያነት ተመርጠዋል፡፡ ለጥናቱ በሚመች መልኩም ተዘጋጅተዋል፡፡ የጥናቱ ተሳታፊዎች በባሕር ዳር ከተማ በፋሲሎ አጠቃላይ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በ2004 ዓ.ም. የ10ኛ ክፍል ትምህርታቸውን በመከታተል ላይ ያሉ ተማሪዎች ናቸው፡፡ ተማሪዎቹ የተመረጡት ከዕድል ሰጭ የንሞና ዘዴ ውስጥ በቀላል የዕጣ ንሞና አመራረጥ ዘዴ (simple random Sampling) ነው፡፡ ብዛታቸውም 270 ነበር፡፡ በጥናቱ ዋነኛው የመረጃ መሰብሰቢያ መሣሪያ መጠይቅ ሲሆን የተማሪዎች የአንብቦ መረዳት ችሎታ ውጤትም በፈተና አማካኝነት ተገኝቷል፡፡ በመጠይቁ የተካተቱት 25 ጥያቄዎች ናቸው፡፡ እነዚህም በመስኩ በተለያዩ ጊዚያት ምርምሮችን ያካሄዱት ሮዲና አሌክሳንደር (1980) ካዘጋጁት መጠይቅ የተውጣጡ ናቸው፡፡ ጥያቄዎቹን ለጥናቱ በሚያመች መልኩ ወደ አማርኛ አሻሽሎ በመተርጎም የማንበብ አመለካከትን እንዲለኩ ተዘጋጅተው ሥራ ላይ ውለዋል፡፡
የፅሁፍ መጠይቁ የአማካሪ ማስተካከያ ታክሎበትና በሙከራ ጥናት ተፈትሾ አስተማማኝ ሆኖ በመገኘቱ ለጥናቱ የሚፈለጉት መረጃዎች ተሰብስበውበታል፡፡ የአንብቦ መረዳት ፈተና ጥያቄዎቹም በአማካሪውና በአማርኛ መምህር ማስተካከያ ተደርጎባቸው በሙከራ ጥናት ተፈትሸው አስተማማኝ ሆነው በመገኘታቸው የጥናቱ ተሳታፊ ተማሪዎችን የአንብቦ መረዳት ችሎታ ለመለካት ተግባራዊ ተደርገዋል፡፡ በመጠይቅና በፈተና የተሰበሰቡት መረጃዎችም የተለያዩ ገላጭና ተንባይ ስታስቲካዊ ዘዴዎችን በመጠቀም ተተንትነዋል፡፡

በመጠይቅ አማካኝነት የተሰበሰበውን መረጃ መሠረት በማድረግ የመጀመሪያው መሪ ጥያቄ  በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ተዛምዶ አለ? የሚለው ነበር፡፡ ከዚህ አንፃር የማንበብ አመለካከት ከአንብቦ መረዳት ችሎታ ጋር ተዛምዶ እንደሌለው የትንተናው ውጤት አመልክቷል፡፡  

በሁለተኛ ደረጃም የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታቸውን የመተንበይ ድርሻው ምን ያህል ነው? የሚለውን ጥያቄ ለመመለስ በተደረገው ጥረት ቀላል የድኅረት ትንተና ተግባራዊ ሆኗል፡፡ በትንተናው መሠረትም የማንበብ አመለካከት በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ላይ ያለው ድርሻ (R² = 0.003፣ F = 0.762፣ P>0.05) ሲሆን፣ ይህም ተለዋዋጩ በተማሪዎች የአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ጉልህ ድርሻ ወይም አስተዋፅኦ እንደሌለው አመልክቷል፡፡ (Beta Coefficient) ተሰልቶ የተገኘው ውጤት እንዳመለከተው ደግሞ የማንበብ አመለካከት በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ላይ ያለው ድርሻ ተንባይ አለመሆኑን ነው፡፡ በተጨማሪም የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ቀጥተኛ ተፅዕኖ በስታትስቲክስ ጉልህ ድርሻ የለውም፡፡

በሦስተኛ ደረጃ የተመረመረው መሠረታዊ ጥያቄ  በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ያለው ተዛምዶ በፆታ ልዩነት ያሳያል? የሚለው ነበር፡፡ በዚህ ረገድ ሴት ተማሪዎች ለማንበብ ያላቸው አመለካከት በአማካይ ውጤት ከወንድ ተማሪዎች አማካይ ውጤት በስታትስቲክስ ጉልህ ብልጫ ቢያሳይም ልዩነቱ ጉልህ ባለመሆኑ የጎላ ልዩነት አለ ለማለት አያስደፍርም፡፡ ከዚህ በተጨማሪ የሴቶቹ አንብቦ የመረዳት ችሎታ ከወንዶቹ በስታትስቲክስ ጉልህ ብልጫ ቢያሳይም ልዩነቱ ጉልህ ባለመሆኑ ልዩነት አለ ለማለት አይቻልም፡፡

በአጠቃላይ የጥናቱ ትንተና ውጤት እንዳመለከተው የተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶ የላቸውም፡፡ የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታን የመተንበይ ድርሻው ጉልህ አይደለም፡፡ በተጨማሪም የሴቶች የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ በስታትስቲክስ ከወንዶቹ ተማሪዎች ብልጫ እንዳለው ቢያሳይም ልዩነቱ ጉልህ ባለመሆኑ ልዩነት አለው ለማለት አያስደፍርም ፡፡
5.2. መደምደሚያ
የጥናቱን ትንተናና ማብራሪያ መሠረት በማድረግ ከሚከተሉት መደምደሚያዎች ላይ ተደርሷል፡፡
1.  በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ተዛምዶ የለም፡፡
2.  የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታቸውን የመተንበይ ጉልህ ድርሻው ወይም አስተዋፅኦ የለውም፡፡
3.  የማንበብ አመለካከት የአንብቦ መረዳት ችሎታ ላይ ቀጥተኛ ተፅዕኖ በስታትስቲክስ ጉልህ ድርሻ የለውም፡፡
4.  በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ያለው ተዛምዶ በፆታ ልዩነት ቢያሳያይም ልዩነቱ ጉልህ ባለመሆኑ ልዩነት አለ ለማለት አያስችልም፡፡
5.3.መፍትሔ
በዚህ ጥናት የተደረሰባቸውን ግኝቶችና ውጤቶች ተግባራዊ ለማድረግ እንዲሁም የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከት ለማጐልበት እንዲቻል የሚከተሉት መፍትሔዎች ተጠቁመዋል፡-
  1. በጥናቱ የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት በአንብቦ የመረዳት ችሎታ ያለውን የትንበያ መጠን መገንዘብ ስለተቻለ መምህራኑ ይህንኑ በመረዳት የመማሪያ ክፍል የትምህርት አቀራረባቸው የማንበብ አመለካከትን የሚያሳድግ ብቻ  ሳይሆን  ሌሎችንም ዘዴዎች በአማራጭነት  ቢጠቀሙ፡፡
  2. ጥናቱ በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ያለው ተዛምዶ በፆታ ልዩነት እንዳለው ስለሚያሳይ ወላጆች የልጆቻቸውን የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ በመገንዘብ ለችግሮቻቸው ከመምህራን ጋር በመተባበር መፍትሄ ቢፈልጉ፡፡
3.  የትምህርት ባለሙያዎች በጥናቱ ግኝቶች መረጃ መሠረት የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ በመገንዘብ መምህራን የትምህርት ዕቅድ፣ መርሐ ትምህርትና የንባብ ትምህርት መርሐ ግብር ሲያዘጋጁ የተማሪዎቹን የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ ከማጎልበት አንፃር እንዲመለከቱት ቢጠቁሙ፡፡
4.  በርዕሱ ዙሪያ ተጨማሪ ጥናት የሚያደርጉ ተመራማሪዎች ይህንን ጥናት እንደ መነሻ በማድረግ ከዚህ የተሻለ ጥናት ለማካሄድ ጥረት ቢያደርጉ፡፡ የሚሉት በአጥኝው የቀረቡ የመፍትሄ ሐሳቦች ናቸው፡፡











ዋቢዎች
መሐመድ ዓሊ፡፡ (1992 ዓ.ም)፡፡ ‘‘በባሕር ዳር ከተማ የግዩን ከፍተኛ ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ10ኛ ክፍል ተማሪዎች የአማርኛ ቋንቋን ለመማር ያላቸው አመለካከት፡፡'' ለሁለተኛ ዲግሪ ማሟያ የቀረበ ፅሁፍ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ፡፡ (ያልታተመ)፡፡
መስፍን ኃብተማሪያም፡፡ (2001) የቡና ቤት ስዕሎችና ሌሎችም ወጐች (1976-1999)፡፡ ኤማይ ፕሪንተርስ ኃ.የተ.የግ.ማ፡፡ አዲስ አበባ፡፡
በዓሉ ግርማ፡፡ (2001)፡፡ የሕሊና ደወል፡፡ (2ኛ ዕትም)፡፡ ፋር ኢስት ትሬዲንግ፡፡ አዲስ አበባ፡፡
ባሕሩ ዘወዴ፡፡ (2001)፡፡ የኢትዮጵያ ታሪክ ከ1847 እስከ 1983፡፡ አዲስ አበባ ዩንቨርስቲ ፕሬስ፡፡ አዲስ አበባ፡፡ 
ታፈረ ወርቁ፡፡ (2000)፡፡ ‘‘በዳንግላ ከፍተኛ 2ኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የ9ኛ ክፍል ተማሪዎች የንባብ ዳራና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶ፡፡'' ለሁለተኛ ዲግሪ ማሟያ የቀረበ ፅሁፍ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ፡፡ (ያልታተመ)፡፡
ታዛሽ ሰይፉ፡፡ (1992 ዓ.ም)፡፡ ‘‘የ11ኛ ክፍል ተማሪዎች የአንብቦ መረዳት ችሎታ፡፡'' ለመጀመሪያ ዲግሪ ማሟያ የቀረበ ፅሁፍ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ፡፡ (ያልታተመ)፡፡
ደምሰው አሰፋ፡፡ (1995)፡፡ ‘‘በ10ኛ ክፍል የአማርኛ መማሪያ መፀሐፍ ውስጥ የሚገኙ ምንባቦች የተማሪዎችን የማንበብ ፍላጎት ለመያዝ ያላቸው ብቃት፡፡'' ለመጀመሪያ ዲግሪ ማሟያ የቀረበ ፅሁፍ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ፡፡ (ያልታተመ)፡፡
ገደፋው አምሳሉ፡፡ (1993)፡፡ ‘‘የ11ኛ ክፍል ተማሪዎች አማርኛ ቋንቋን ለመማር ያላቸው ተነሳሽነትና የትምህርት ውጤት ተዛምዶ፡፡'' ለመጀመሪያ ዲግሪ ማሟያ የቀረበ ፅሁፍ፣ ባሕር ዳር ዩኒቨርስቲ፡፡ (ያልታተመ)፡፡
Abu-Rabia, S. (1996). Attitudes and cultural background and their relationship to reading comprehension in a second language: a comparison of three different social contexts. International Journal of Applied Linguistics, 6: 81–105. Doi: 10.1111/j.1473-4192.1996.tb00090.x
Aebersold, J.A., and Field, M.A. (1997). From Reader to Reading Teacher: Issues and strategies for second language classrooms. Cambridge Universty Press.
Alexander, J.E., and Filler, R.C. (1976). Attitudes and Reading. Newark., DE. International Reading Association.
Appllegate, A.J. and Appllegate, M.D. (2004). The Peter Effect: Reading Habits and Attitudes of Preservice Teachers. The Reading teacher, 57, 554-563.
Bas, G. (2012). Correlation between elementary students’ reading attitudes and their writing dispositions. IJGE: International Journal of Global Education - 2012, volume 1 issue 2.  Konya University. Graduate School of Education Sciences.   Konya, Turkey
Blackb, A. (2006). Attitudes to Reading: An Investigation across the Primary Years. Thesis.Master of Education, School of Education, Australian Catholic Universty.
Block, C.C. (1997). Teaching the Language Arts: Expanding Thinking through Student Centered Instruction .Boston: Allyn and Bacon.
Bokhorst-Heng, W. and Pereira, D. (2008), Non-at-risk adolescents' attitudes towards reading in a Singapore secondary school. Journal of Research in Reading, 31: 285–301. Doi: 10.1111/j.1467-9817.2008.00369.x
Christina, C. and Jonathan D. (2011). Young People's Reading and Writing: An In-Depth Study Focusing on Enjoyment, Behavior, Attitudes and Attainment. 2011-00-00.
Cramer, M. (1994). Fosternig the Love of reading: The Affective Domain in Reading Education (PP.74-87).Newyork, DE: International reading Association.
Day, R. and Bamford. (1998). Extensive Readng and In The Second Language Classroom. U.S.A : Cambridge Universty Press.
Dornyei, Z. (2001). Motivational Strategies in the Language Classroom. Cambridge: Cambridge Universty Press.
Dubin, B.V, and Zorkaia, N.A (2010). The changes in the attitude of Russia's Reading public interms of frequency and intensiveness. Russian Education and Society, v52n7 P16-51 Jul. 2010.
Eiser, J. R., (1994). Social Psychology. Attitudes, cognition and social behavior. Cambridge University Press.
Estes, T. H. (1971). A Scale to Measure Attitudes Toward Reading. Journal of reading. 15, 135-138.
Evans, K.M., (1965). Attitudes and Interests in Education. Routlege and Kegan private limited.
Feldman,R.S.,(1996). Understanding Psychology. (4th Ed). McGraw-Hill, Inc.
Feldman,R.S (1999). Understanding Psychology. (5th Ed). McGraw-Hill, Inc.
Frankel, J.R., and Wallen. (2000). How to design and Evaluate Research in education. (4th Ed). Mcgraw Hill.  
Flood J., and. Lapp, D., (1983). Teaching Reading to Every Child. (2nd Ed.). Macmillan publishing Co., Inc.
Gambrell, L.B.,(1996). Creating Classroom Cultures That Foster Reading Motivation. The Reading Teacher, 50, 14-25.
Graves, M.F., Laberge, M.J. and Cooke C. (1983). Efects of previewing difficult short stories on low ability junior high school students comprehension, recall and attitudes. Reading Research QuarterlyVol. 18, No. 3, spring, 1983  
Greaney, V. and Hegarty, M. (1987). Correlates of leisure-time reading. Journal of Research in Reading, 10: 3–20. Doi: 10.1111/j.1467-9817.1987.tb00278.x
Kulik, A.J. and Kulik C.C. (1982). Effects of Ability Grouping on Secondary School Students:  A Meta-analysis of Evaluation Findings. American Educational Research Journalaer.sagepub.com. Doi: 10.3102/00028312019003415. Am Educ Res J September 21, 1982 vol. 19 no. 3 415-428 University of Michigan.
Kush, J.C, and Watkins, M.W. (1996). Long –Term Stability of Children's Attitudes Toward Reading. [Eelectronic Version]. The Journal of Educational Reserch.
Heathington, B.S. and Alexander, J.E. (1984). Do Classroom Teachers Emphasize Attitudes Toward Reading?.The Reading Teacher, 37, 484-488.
Heaton, J.B. (1990). Writing English Language Test. London: Longman.
Heilman, A.W. Blair,T.R.,and Ruphley W.H. (1998). Principles and Practices of Teacing Reading. (9th Ed.).New Jersy prints Hall Inc.

 Lena S.and, Karin T. ( 2007). Influences of Family Based Prerequisites, Reading Attitudes, and Self-Regulation onReading Ability.Contemporary Educational Psychology, v32 n2 p206-230 Apr 2007 Journal of Atricles; Reports – Research.

 Logna, S., and Johnston, R. (2009). Gender Differences in Reading Ability and Attitudes: Examining where these differences Lie. Jornal of Research in Reading, V32 n2 P199-214 May 2009.
Lorene, W.C., (2010). ‘‘Secondary Students' Reading Attitudes and Achievement in a scaffold Silent Reading Program Versus Traditional Sustained Silent Reading.’’ ProQuest LLC, Ph.D.Dsessertaion, Auburn University.
Lynn, H.W. (2010). Difference between third, forth, and fifth Grade students' attitudes to ward reading in relation to community size. Master of education (MED), Bowling Green state Universty, reading 2010.
Madsons, H.S. (1983).Teachniques In Testing. Newyork: Oxford Universty Press.
Martinez, R.S., Tolga, A.o, and Jermy, J. (2008). Influence of Reading Attitude on Reading Achievement: A Test of the Temporal Interaction Model. Psychology in the schools, v45 n10 P1010-1022. Dec.2008.
May, B.F. (1990). Reading as Communication: An Interactive Approach. (3rd Ed.). U.S.A: Macmillan Publishing Company.
Mckenna, M.C., Kear, D.J., and Ellsworth, R.A., (1995). Children’s attitudes to woard reading.A national survey. Reading research quarterly. Retrieved on 01/08/2011 09:59. From http:// WWW.jstor. Org /stable/748205.
Muller, D.L., (1973). Teacher Attitude Towards reading. Journal of Reading. 17, 202-205.
Myers, G.D. (1999). Social Psychology. (6th Ed). The McGraw-Hill Componies, Inc.
Norton,D.E.(1997). The Effective Teaching of Language Arts. (5th Ed.).New Jersy: Prentice Hall Inc. 
Nancy,W.(1989).‘‘ Developmental relationships between Students’ attitudes Toward reading and Reading Achivement In Grades 1 through 8’’. Page 95, Education Specialist Thesis, Universty of Northen Iowa.
Ransbury, M.K. (1973). An Assesment of Reading Attitude. Journal of Reading, 17,25-28.
Rasinski, T., and Padak, N, (1996). Holistic Reading Strategies Teaching Children who Find  Reading Difficult. Prentice Hall, Inc.
 Roe, B.D., and Smith, S.H., (2005). Teaching reading in today's middle schools, Houghton Mifflin Company.
Rrowell, G.C., (1972). An Investigation of Factors Related to Change in Attitude Toward Reading. 972-73* Vol.5,No.4,Fall.
Sallabas, M.E., (2008). Relationship between 8th Grade Secondary School Students' Reading Attitudes and Reading Comprehension skills. Journal of the Faculty of Education. V01, 9, Issue.16 (fall 2008). 141-155. Retrived on http://WWW.web. Inonu. Edu.tr/ efdergi/ sayi 16/08-Rn.pdf.
Schmitt,E.(2009). ‘‘Four Case studies:The reading Attituds and Practices of Teachers and students Grade’’.Thesis,Master of Education in Reading,The graduate College of Bowling Green State Universty.
Skinner, C.E.,(1998). Educational Psychology. (4th Ed).  Prentice-Hall, Inc.

Spiegel, D.L. (1994). A Portrait of Parents of successful readers. In E.H.NewYork ,DE: International Reading association.

Thraves, P., (2010). "An Investigation into Students' Reading Attitudes and Habits Using a Children's Literature Intervention Programme" CPUT Thesis and Dissertations. Paper 296. http://dk.cput.ac.za/td_cput/296

 Theodore S.K. (2010). Reading Achievement, Attitudes towards, Reading and Reading Self-Esteem of  Historically Low Achieving  Students  Journal of Instructional Psychology, v37 n2 p184-188 Jun 2010.Journal Articls; Reports – Research.

 Vacca, R.T.And Vacca, J.L.,(1999). Content Area Reading Literacy and Learning across the Curriculum. (6th Ed). Long Man.
Webb, H.L., (2009). ‘‘The Relationship between African American Middle School Students' attitudes toward Reading and their Reading Comprehension Level’’.  Proquest LLC, Ed.D. Unpublished Dissertation, the University of Memphis.
Wie (Veronica) (2009). ‘‘Gender Difference in Reading Comprehension for Chinese Secondary School Students.’’ A Seminar Paper Research. Master of Science in Education. Unpublished Thesis. The Graduate Faculty Universty of Wisconsin-Platteville.
 Yaacov, P. (2010). A Meta- Analysis of the Relationship between Student Attitudes towards Reading and Achievement in Reading. Journal of Research in Reading, v33 n4 P335-355 Nov 2010.
Zelalem Berhanu. (2010). ‘‘The Reading Attitudes Preferences and Habits of First Year Bahir Dar Universty Studentes with Particular Reference To The faculty of Humanities.’’  Unpublished Master’s Thesis. Humanities Faculty, Bahir Dar Universty.
   

አመለካከትና የማንበብ አመለካከት ቅርብ ግንኙነት እንዳላቸው የሚጠቁሙ ጥናቶች በ ሐሰን መሐመድ ሐሰን


ምዕራፍ ሁለት፡- ክለሳ ድርሳን
2.1.አመለካከትና የማንበብ አመለካከት ግንኙነት
አመለካከትና የማንበብ አመለካከት ቅርብ ግንኙነት እንዳላቸው የሚጠቁሙ ጥናቶች አሉ፡፡ ዴይና ባምፎርድ (1982) በጥናታቸው እንደገለፁት አመለካከቶች ሰዎች አንድን ተግባር እንዲያከናውኑ ወይም እንዳያከናውኑ የሚያደርጉ ናቸው፡፡ አዎንታዊ አመለካከቶች አንድን ነገር ለማድረግ የሚያነሳሱ ሲሆኑ፣ በተቃራኒው አሉታዊ አመለካከቶች አንድን ተግባር በንቃት ለማከናወን  ተነሳሽነትን ይቀንሳሉ፡፡ በተመሳሳይ የማንበብ ተግባርም ግለሰቦች ለማንበብ ባላቸው አመለካከቶች አማካኝነት ተፅዕኖ ይደርስበታል፡፡ የማንበብ አመለካከታቸው አዎንታዊ የሆነ አንባቢያን ማንበብን መለማመድ ሲያፈቅሩ፣ ለማንበብ አሉታዊ አመለካከት ያላቸው ማንበብን ከመጥላታቸውም በላይ በማንበብ ተግባራት ለመሳተፍ ፈቃደኛ አይደሉም፡፡ ይህ የሚያመለክተው አመለካከትና የማንበብ አመለካከት ጥብቅ ቁርኝት እንዳላቸው ነው፡፡
ከዚህ ጋር ተመሳሳይ የሆነ ጥናት ያደረጉት ኮንሊ (1992) እንዳብራሩት የማንበብ አመለካከት ተማሪዎች አንድን ንባብ ለማንበብ ወይም ላለማንበብ ያላቸው ስሜት ሲሆን፣ ይህንን ተፅዕኖ የሚያሳድረው ደግሞ አመለካከት ነው፡፡ በተጨማሪም አዎንታዊ የማንበብ አመለካከት ስኬታማ ማንበብን ሲያጎናፅፍ አሉታዊ የማንበብ አመለካከት አንባቢያን ደካማ ፍላጎት እንዲኖራቸው ያደርጋል፡፡ አሌክሳንደርና ፊለር (1992) ጨምረው እንዳስረዱት ተማሪዎች ለማንበብ ያላቸው አመለካከት አዎንታዊ ከሆነ የማንበብ ችሎታ ውጤታቸው ስለሚጨምር ብዙ ያነባሉ፡፡ በተቃራኒው ደግሞ የማንበብ አመለካከታቸው አሉታዊ ከሆነ ውጤቱ የተገላቢጦሽ ይሆናል፡፡
ሮኢና ስሚዝ (2005) እንዳብራሩት ደግሞ ተማሪዎች ንባብን ለመማር ተግባራትን ሲያከናውኑ በሂደቱ ላይ ተፅዕኖ ከሚያሳድሩት ነገሮች ዋነኞቹ የማንበብ አመለካከቶች ናቸው፡፡ በዚህም መሠረት የቀረበላቸውን ምንባብ ለማንበብ በጐ አመለካከት ያላቸው ተማሪዎች ንባብን ለመማር ብርቱ ጥረት ሲያደርጉ፣ በጐ ያልሆነ አመለካከት ያላቸው ግን በሂደቱ ለመሳተፍ እንቅስቃሴያቸው ዝቅ ያለ ነው፡፡
ተመሳሳይ ጥናት ያቀረቡት ኮንሊ (1992) እና ሜይ (1990) እንዳመለከቱት የተማሪዎችን የማንበብ አመለካት አዎንታዊ ወይም አሉታዊ የሚያደርጉት መምህራን ናቸው፡፡ ለምሳሌ መምህራኑ በመማሪያ ክፍል ውስጥ አዎንታዊ የማንበብ አመለካከትን የሚያጎለብቱ ልምዶችን ለተማሪዎች ካስተዋወቁ፣ ተማሪዎቻቸው ምቹ ሁኔታዎችን በመፍጠር፣ ያነበቡዋቸውን መፅሄት፣ መፀሐፍና መጣጥፍ ወደ መማሪያ ክፍላቸው ይዘው እያመጡ ካነበቡላቸው የተማሪዎቹ የማንበብ አመለካከት አዎንታዊ ይሆናል፡፡
በተመሳሳይ ሙለር (1973) የተባሉት ተመራማሪ በበኩላቸው የማንበብ አመለካከትን ለመለካት በ41 ተማሪዎች ላይ ቅኝት አድርገው ነበር፡፡ የጥናቱ ውጤት  እንደሚያመለክተው የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከት በከፍተኛ ሁኔታ ለተፅዕኖ የሚያጋልጠው የመምህራን የማንበብ አመለካከት ነው፡፡ በማንኛውም ክስተት መምህራን የተማሪዎቻቸውን የማንበብ አመለካከት ከተረዱና ከተቀበሉት ለውጥ ያመጣሉ፡፡ ይህንን በሚመለከት ተመሳሳይ ጥናት ያደረጉት ሞዩር (1977) የማንበብ አመለካከትን ከመምህራን የማንበብ ልምድ ጋር አያይዘውታል፡፡ በተጨማሪም መምህራን አዘውትረው የሚያነቡ ከሆነ ተማሪዎቻቸውም የማንበብ አመለካከታቸው አወንታዊ እንዲሆን አርአያ ይሆናሉ፡፡ ይህንን በምርምር ለማረጋገጥ በተደረገው ጥናት አዘውትረው ከሚያነቡና ከማያነቡ መምህራን በመጠይቅ የተሰበሰበው መረጃ ውጤት እንዳመለከተው አንባቢ መምህራን ከማያነቡት በተሻለ ለተማሪዎች የማንበብ አመለካከት አርዓያ ሆነው ተገኝተዋል፡፡
ከዚህ በተለየ ኢስቴስ (1971) የተባሉት ተመራማሪ ተማሪዎች የማንበብ አመለካከታቸው የሚለወጥበትን ምክንያት ለማወቅ ጥናት አድርገዋል፡፡ ይህንንም ዕውን ለማድረግ የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከት መለኪያ መጠይቅ አዘጋጅተው ነበር፡፡ በጥናቱ ከሶስተኛ እስከ 12ኛ ክፍል ከሚማሩ ተማሪዎች መካከል ናሙና በመውሰድ የማንበብ አመለካከታቸውን ለክተዋል፡፡ ከትንተናው የተገኘው ውጤት እንዳመለከተው ማንበብን በተመለከተ የወጣት ተማሪዎች አመለካከት አወንታዊ ነው፡፡
ከዚህ ምርምር ጋር የሚቃረን ጥናት ያቀረቡት ተመራማሪ ራንስበሪ (1973) ናቸው፡፡ ተመራማሪው በጥናታቸው 65 የጥናት ተሳታፊ ተማሪዎችን፣ መምህራንና ወላጆችን በመምረጥ ለማንበብ የሚያስደስታቸውንና የማያስደስታቸውን ንባብ  እንዲገልፁ አድርገዋል፡፡ ተማሪዎቹ አንድን ንባብ እንዲያነቡና እንዳያነቡ የሚገፋፉት በንባብ መማሪያ  መፃህፍት አማካኝነት መሆኑን አመላክተዋል፡፡ ወላጆች ንባብን እንዲጠሉት ያደረጋቸው ምክንያት አዘውትረው አለማንበባቸው ነው፡፡ መምህራን በበኩላቸው የማንበብ አመለካከት አወንታዊና አሉታዊ እንዲሆን የሚያደርገው የተማሪዎች አዕምሯዊ ችሎታ ሊሆን ይችላል ብለዋል፡፡ በጥናቱ ማጠቃለያ ላይ የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከት ተፅዕኖ የሚያሳድርበት ዋነኛ ምክንያት የንባብ ችሎታ መሆኑ ተረጋግጧል፡፡
ሒዚግነቶንና አሌክሳንደር (1984) ባካሔዱት ጥናት ደግሞ አወንታዊ የማንበብ አመለካከትን ለማዳበር የመምህራንና የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከት ገምግመዋል፡፡ በጥናቱ 100 መምህራን በማስተማር ልምዳቸው መሰረት ተመርጠው ንባብን በመማሪያ ክፍል ውስጥ ሲያስተምሩ ምን፣ ምን ተግባራትን እንደሚያከናውኑ አጠቃላይ መጠይቅ ቀርቦላቸዋል፡፡ በመጠይቁ ላይ ትኩረት በመስጠት የሚጠቀሙባቸውን 9 የማስተማር ልምዶችን በቅደም ተከተል እንዲዘረዝሩ ተጠይቀዋል፡፡ በመጠይቁ የቀረቡላቸው ዝርዝሮችም አንብቦ መረዳት፣ ቃላዊ ንባብ፣ የዝምታ ንባብ፣ ቃላዊ ትርጉም፣ ቃላትን መምረጥ፣ መዋቅራዊ ትንተና፣ የማንበብ አመለካከቶችና የክህሎት ጥናት የሚሉ ነበሩ፡፡ ከመጠይቁ የተገኘው ውጤት እንዳመለከተው በርካታዎቹ መምህራን የማስተማሪያ ክፍለ ጊዚያቸውን ለማንበብ አመለካከት ማጎልበቻነት አይመድቡም፡፡ ምክንያቱም ደግሞ መምህራኑ ክህሎትን በማስጨበጥ ላይ ስለሚያተኩሩና የክህሎት እድገት የማንበብ አመለካከትን አዎንታዊና አሉታዊነት ለመጨመርና ለመቀነስ አስተዋፅኦ ያበረክታል ብለው ስለሚያምኑ ነው፡፡
ማና እና ማይሽፍ (1987) ከላይ ያለውን ጥናት በመቃረን ባደረጉት ጥናት በዩኒቨርስቲ የስነ-ፅሁፍ ተማሪዎች ለምን ለአሉታዊ የማንበብ አመለካከት እንደተጋለጡ መርምረዋል፡፡ ምክንያቱንም ለመገንዘብ ጥረት አድርገዋል፡፡ ጥናቱን ተግባራዊ ለማድረግ በጥቅም ላይ የዋለው የመረጃ መሰብሰቢያ መሳሪያ ተማሪዎቹ ግለ ታሪካቸውን እንዲሞሉ በማድረግ ነበር፡፡ ከተማሪዎቹ ግለ ታሪክ በዳግም ግምገማ ከተገኘው ውጤት ለመረዳት እንደተቻለው በተማሪዎቹ ላይ አሉታዊ የማንበብ ተፅዕኖ ያሳደረው የተማሪዎቹ ወላጆችና መምህራን አርዓያ በመሆን የማንበብ አመለካከታቸው እንዲጎለብት ድጋፍ ስላላደረጉላቸው ነው፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ሞሪሰን፣ ጃኮብስና ስዊንያርድ (1999) መምህራን በመማሪያ ክፍል ውስጥ ለተማሪዎቻቸው የሚያነቡላቸው ግላዊ የመዝናኛ ንባብ የተማሪዎችን የማንበብ አመለካከት ለመለወጥ ያለውን ፋይዳ በሚመለከት አጥንተዋል፡፡ በመጠይቅ ከተሰበሰበው የማስተማርና ግላዊ የንባብ ልምድ መረጃ ከተገኘው ውጤት ለመረዳት እንደተቻለው መምህራን በአብዛኛው የሚያነቡት የሚያስተምሩትን ትምህርት መፃሕፍት ንባቦችን ብቻ ነው፡፡ በዚህም ምክንያት ተማሪዎቹ ማንበብን መሰረት በማድረግ እየተዝናኑ ስለማይማሩ ለማንበብ ያላቸው አመለካከት ከአዎንታዊ ይልቅ አሉታዊ ወደ መሆን አዘንብሏል፡፡
አፕሊጌትና አፕሊጌት (2004) ያደረጉት ጥናት የመምህራንን የማንበብ ልምዶችና አመለካከቶች የሚመርምር ነው፡፡ በልቅ መጠይቅ አማካኝነት በመምህራን ላይ በተደረገው ቅኝት 54% የሚሆኑት መምህራን የማንበብ ጉጉት የሌላቸው መሆናቸውን ጥናቱ አመልክቷል፡፡ ለዚህም ምክንያት ሳይሆን አይቀርም ተብሎ የተገመተው መምህራኑ በቀድሞ የትምህርት ዘመናቸው ወቅት የማንበብ አመለካከታቸው አሉታዊ ተፅዕኖ አድሮበት ስለነበር ነው፡፡ በጥናቱ ማጠቃለያ  ላይ እንደሰፈረው የመምህራን ማንበብን ያለመውደድ ልምድና የአመለካከት አለመዳበር የተማሪዎቻቸውን የማንበብ አመለካከት በዕጅጉ እንደሚጎዳ ተገልጧል፡፡
የብላክቢ (2006) ጥናት ከአፕሊጌትና አፕሊጌት (2004) የተለየ ነው፡፡ ተማሪዎች እንደሚኖሩበትና እንደተማሩት አግባብ የማንበብ ክሕሎታቸው ዕድገት ለተፅዕኖ ይጋለጣል፡፡ በማንበብ አመለካከቶች ላይ አወንታዊና ወይም አሉታዊ ተፅዕኖ ለማድረስ ምክንያት የሚሆኑት ጉዳዬች ተፈጥሮ (innate) ፣ ቤተሰብና ትምህርት ቤት ናቸው፡፡ እነዚህ የተፅዕኖ ምክንያቶች ተማሪዎች ለማንበብ በሚነሳሱበት ወቅትና ራሳቸውን እንደ አንባቢ መቁጥር በሚጀምሩበት ጊዜ ማንበብን እንዲወዱ ወይም እንዲጠሉ የሚያደርጉ ናቸው፡፡
ብላክቢ (2006) ጨምረው እንደገለፁት፣ ቤተሰብ በማንበብ ላይ አንዳንድ ተፅዕኖዎች ያሳድራል፡፡ ማህበራዊ መደቦችና የቤተሰብ ባሕል የተማሪዎች ማንነት ላይ ጫና በመፍጠር ተፅዕኖ የሚያሳድረው አመለካከታቸውና የንባብ ተግባራቶች ላይ ነው፡፡ ተማሪዎች በቤተሰባቸው አማካኝነት የማንበብና የመፃፍ ችሎታቸው ሲያድግ አመለካከታቸውም አብሮ ያድጋል፡፡
ሞሮውና ያንግ (1997) በተመሳሰይ እንዳጠኑት ወላጆች በመኖሪያ ቤት ልምዶቻቸው በልጆቻቸው ላይ ተፅዕኖ እንዲሚያሳድሩ ያምናሉ፡፡ የቀን ተቀን የቤተሰብ ተግባራት በልጆች የማንበብ ዕድገት፣ በአመለካከቶቻቸውና በማንበብ ተግባራት የተሳትፎ ፍላጎታቸው ላይ የሚያሳድረው ተፅዕኖ ቀላል አይደለም፡፡ ወላጆች ወይም ልጆችን ተንከባካቢዎች መልካም አርዓያ በመሆን ተፅዕኖ ለማሳደር የሚችሉበት ምክንያት ልጆቻቸው በማንበብ ልምምድ ወቅት ምን፣ እንዴት፣ መቼና ለምን እንደሚያነቡ ስለማያስረዷቸው ነው፡፡
ይሁን እንጁ ማዩንግሱንና ሒኪዩንግ (2002) ባደረጉት ጥናት የማንበብና የአመለካከት ዕድገት የሚመጣው በትምህርት ቤት ብቻ የሚመስላቸው በርካታ ወላጆች እንዳሉ አረጋግጠዋል፡፡ በእርግጥ በቤተሰብ ብቻ ሳይሆን፣ በትምህርት ቤት አማካኝነትም በማንበብ አመለካከት ላይ ተፅዕኖ የሚያሳድሩ ሁኔታዎች አሉ፡፡ አዩናላና ሌሎች (2002) በትምህርት ቤት ውስጥ የማንበብ አመለካከትን ለተፅዕኖ የሚያጋልጡ ናቸው በማለት የዘረዘሯቸው፡- ተማሪዎችን በመማሪያ ክፍል ውስጥ ለመዝናናት ማስነበብ፣ በራሳቸው ምርጫ ፅሁፎችን እንዲያነቡ ማድረግና በክፍል ውስጥ ለጓደኞቻቸው ድምፃቸውን ከፍ አድርገው ማስነበብ ናቸው፡፡
ጋምብሪል (2004)፣ በጥናታቸው ግኝት እንደደረሱበት መምህራን ተማሪዎችን አዝናኝ ንባቦች መርጠውላቸው ማስነበብ የማንበብ አመለካከታቸው አወንታዊ ቅርፅ እንዲይዝና የራስ ግላዊ ውጤታማነታቸው እንዲጨምር ያደርጋል፡፡ ተማሪዎቹ በመደበኛነት የመዝናኛ ንባብ የሚያነቡ ከሆነ በስፋትና በጥልቀት ማንበብ እንዲለምዱ፣ የማንበብ ክህሎት ብቃታቸው እንዲያድግ፣ የአንብቦ መረዳትና የቃላት ችሎታቸው እንዲጨምር ያደርጋል፡፡ በተጨማሪም ምናባቸውን ለማስፋት፣ የፈጠራና የክህሎት ዕድገታቸውን ከፍ ለማድረግ ይረዳል፡፡ የጉዝሪ (1999) የጥናት ውጤት ከጋምብሪል (2004) ጋር ይቃረናል፡፡ ተማሪዎች በራሳቸው ምርጫ ብቻ  የመዝናኛ ፅሁፎች ወይም ድርሳናትን መርጠው ማንበባቸው ከራሳቸው ፍላጎትና አመለካከት ጋር የሚገጣጠም ርዕስ እንዲያነቡ ስለሚያደርጋቸው በራሳቸው ሙከራዎች ስሌት ዕውቀትና ልምዶቻቸውን በማስፋት ግላዊ ዓላማቸውን ለማሳካት ያገለግላቸዋል፡፡
ከዚህ ጥናት በተለየ ድሪኸር (2003) እንደገለፁት ተማሪዎች ድምፃቸውን በመማሪያ ክፍል ውስጥ ከፍ አድርገው እንዲያነቡ ማድረግ አወንታዊ የማንበብ አመለካከታቸው እንዲጎለብት ያደርጋል፡፡ ተማሪዎቹን ከንባብ በኃላ በቁልፍ ሐሳቦች ላይ ማወያዬት ፍላጎታቸውን ያጠናክራል፡፡ አወንታዊ የማንበብ አመለካከታቸውን ያሳድጋል፡፡ ብራስል (2003) እንደጠቀሱት ደግሞ የመዝናኛ ምንጭ ይሆናቸዋል፣ የቃላት ክምችታቸው መሰረት ይይዛል፣ ውጤታማ የንባብ ብልሐቶችን ይማራሉ፡፡
በመጨረሻም ስችማይት (2009) እንደሚገልፁት የማንበብ አመለካከትን በሚመለከት   ተመሳሳይና ተቃራኒ ጥናቶች አሉ፡፡ የጥናቶቹ ግኝቶች የማንበብ አመለካከት በወላጆችና በመኖሪያ ቤት አካባቢ፣ በመማሪያ ክፍል እንዲሁም በተማሪዎችና በመምህራን አመለካከትና ባሕሪ ላይ ያተኮሩ ሲሆኑ አመለካከትና የማንበብ አመለካከት ያላቸውን ግንኙነት የሚጠቁሙ ናቸው፡፡
በአጠቃላይ ከተደረጉት ጥናቶች ቅኝት ለመገንዘብ እንደሚቻለው ማንበብና የማንበብ አመለካከት ጥብቅ ግንኙነት አላቸው፡፡ አመለካከት በማንበብ ላይ የሚያሳድረው የራሱ የሆነ ተፅዕኖ አለው፡፡ የማንበብ አመለካከት ተለዋዋጭ ሲሆን፣ ምክንያቶቹም ወላጆች፣ ቤተሰብ፣ መምህራንና አካባቢ የሚያሳድሩት አወንታዊና አሉታዊ ተፅዕኖዎች ናቸው፡፡ ስለዚህም አመለካከትና የማንበብ አመለካከትን ግንኙነት ጠንቅቆ በመረዳት በትምህርት ቤት ውስጥ በተማሪዎች የማንበብ አመለካከት ላይ ለሚፈጠሩ ችግሮች መፍትሄ መፈለግ ያሻል፡፡
2.2. የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች የማንበብ አመለካከት
ኩሊክና ኩሊክ (1982) በሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች በችሎታ አቅም የተደራጀ ቡድን ለአመለካከት ለውጥ ያለውን አስተዋፅኦ በሚመለከት ጥናት አድርገዋል፡፡ ጥናቱ የተካሄደው 52 ተማሪዎችን በከፍተኛ፣ በመካከለኛና በዝቅተኛ ችሎታ ቡድኖች በማደራጀት ነበር፡፡ የጥናቱ ውጤት እንዳመለከተው ተማሪዎችን በቡድን ማደራጀት ለአመለካከት ለውጥ ጠቀሜታ አለው፡፡ በጥናቱ በቡድን የተደራጁት ተሳታፊዎች ለሚማሩት የትምህርት ዓይነት በርካታ አዎንታዊ አመለካከቶችን ሲያሳድጉ፣ በቡድን ያልተደራጁት ግን አመለካከታቸው አሉታዊ ሆኗል፡፡ በቡድን ከተደራጁት መካከልም ከፍተኛ ችሎታ ያላቸው ተማሪዎች አመለካከታቸው ከፍተኛ ሲሆን፣ መካከለኛና ዝቅተኛ ችሎታ ያላቸው የአመለካከታቸው ደረጃ መካከለኛዎቹ መካከለኛ፤ ዝቅተኛዎቹ ደግሞ ወደ ዜሮ የሚጠጋ አመለካከት አስመዝግበዋል፡፡
በተመሳሳይ ሊናና ካሪም (2007) የማንበብ አመለካከት፣ ቤተሰባዊ ቅድመ ሁኔታና በራስ ጥረት መማር በማንበብ ችሎታ ላይ የሚያሳድረውን ተፅዕኖ በሚመለከት ጥናት አድርገዋል፡፡ ጥናቱ የተካሄደው በ4018 የጥናቱ ተሳታፊ የ8ኛ ክፍል ተማሪዎች ላይ መጠይቅና አንብቦ የመረዳት ፈተና በማቅረብ ነው፡፡ ከጥናቱ የተገኘው ውጤት እንደጠቆመው የቃላዊ/የአጠቃላይ ትምህርት በራስ ጥረት መረዳት (Verbal/General academic self-concept) የማንበብ ችሎታ ከፍተኛ ሆኗል፡፡ በተጨማሪም የፆታ ልዩነት በማንበብ አመለካከት ላይ ተፅዕኖ እንዳለውና እንደሌለው ተፈትሿል፡፡ በጥናቱ ውጤት እንገተገለፀው ሴቶቹ ተማሪዎች ከወንድ ተማሪዎች በተሻለ አዎንታዊ የማንበብ አመለካከት አላቸው፡፡ ወንዶቹ ተማሪዎች የተሻሉ ሆነው የተገኙት ትምህርትን በራስ ጥረት በመረዳት፣ በራስ ውጤታማነት፣ በማስታዎስ፣ በማብራራትና በመነሳሳት ናቸው፡፡
በተጨማሪም የሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች አስቸጋሪ አጫጭር ታሪኮችን(ንባቦችን) የማንበብ አመለካከት፣ አንብቦ የመረዳትና የማስታዎስ ችሎታ ለመመርመር ግራቪስ፣ ላበርግና ኩኪ (1983) ጥናት አድርገው ነበር፡፡ ለጥናቱ ተሳታፊ 72 ተማሪዎች በደረጃቸው አንብቦ ለመረደት ቀላልና አስቸጋሪ አጫጭር የንባብ ታሪኮችን በማቅረብ ጥናቱ ተካሂዷል፡፡ የጥናቱ ውጤት እንዳመለከተው አንብቦ ለመረደት ቀላል ለሆኑት ታሪኮች የተማሪዎቹ አመለከካት አዎንታዊ ሲሆን፣ የመረዳትና የማስታዎስ ችሎታቸውም ከ13% እስከ 38% ጨምሯል፡፡
በሌላም በኩል ክሪስቲናና ጆናታን (2011) የታላቋ እንግሊዝ ወጣት ተማሪዎች የማንበብ አመለካከታቸው ለምን እንደቀነሰ ለማወቅ ጥናት አድርገዋል፡፡ በጥናቱ በ17,000 ተማሪዎች ላይ ለማንበብ አመለካከታቸው መቀነስ የትምህርት ቤት የማንበብ ብቃት፣ የፆታ ወይም የጎሳ ልዩነት ምክንያት እንደሆን ቅኝት በማድረግ ባህሪያቸውን ለመመርመር ጥረት ተደርጓል፡፡ በጥናቱ የተገኘው ውጤት እንዳመለከተው የተማሪዎቹ የማንበብ አመለካከት ከ2005 እስከ 2009 ባሉት አምስት ዓመታት  ቀንሶ ተገኝቷል፡፡ ምክንያቱ ደገሞ  ወጣቶቹ በማንበብ ስለማይደሰቱ ማንበብን ማቆማቸው ነው፡፡
በመጨረሻም በትምህርት ውጤታቸው ዝቅተኛ የሆኑ ተማሪዎች ለማንበብ ያላቸውን አመለካከት፣ የማንበብ ችሎታ ውጤታቸውንና በራስ ጥረት ማንበብን በማጐልበት የትምህርት ብቃታቸውን ማሳደግ ይቻልና አይቻል እንደሆን ለመመርመር ቲዎዶር (2010) ጥናት አድርገው ነበር፡፡ ጥናቱን ለማካሄድ በትምህርታቸው ውጤታማ የሆኑ ተማሪዎችን በሁለት ቡድን በማደራጀት አንደኛው ቡድን በንባብ ማሻሻያ መርሐ ግብር (Remedial Reading Program) እንዲሳተፍ ሲደረግ ሌላው ቡድን ግን አልተሳተፈም፡፡ በተጨማሪም ሁለቱም ቡድኖች የማንበብ አመለካከት መጠይቅ እንዲሞሉ ተደርጓል፡፡ የጥናቱ ውጤት እንደጠቆመው በንባብ መፍትሄ መርሐ ግብር የተሳተፉት ተማሪዎች ካልተሳተፉት ጋር ሲነፃፀሩ የማንበብ አመለካከታቸው ተሻሽሏል፣ በራስ ጥረት የማንበብ ውጤታማነታቸው ደረጃው ከፍተኛ ሆኗል፡፡
ለማጠቃለል ያህል ከጥናቶቹ ውጤት ለመገንዘብ እንደሚቻለው የሁለተኛ ደረጃ ትህርት ቤት ተማሪዎች የማንበብ አመለካከት በተለያዩ ምክንያቶች ለተፅኖ ይጋለጣል፡፡ ተማሪዎችን በቡድን ማደራጀት ለአመለካከት ለውጥ ጠቀሜታ አለው፡፡ የማንበብ አመለካከት፣ ቤተሰባዊ ቅድመ ሁኔታና በራስ ጥረት መማር በማንበብ ችሎታ ላይ ተፅዕኖ ያሳድራል፡፡ አንብቦ ለመረደት ቀላል የሆኑ ታሪኮች(ንባቦች) የተማሪዎቹን የማንበብ አመለከካት አዎንታዊ ያደርጋሉ፤ የመረዳትና የማስታዎስ ችሎታን በእጅጉ   ይጨምራሉ፡፡ በማንበብ የማይደሰቱ ተማሪዎች ለማንበብ ያላቸው አመለካከት ዝቅተኛ ይሆናል፡፡ ቢሆንም አመለካከታቸውን በተለያዩ ዘዴዎች በማሳደግ ማሻሻል ይቻላል፡፡
2.3. የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶ
ሳላበስ (2008) በ8ኛ ክፍል ተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ መካከል ተዛምዶ መኖርና አለመኖሩን በሚመለከት ባደረጉት ጥናት የተማሪዎቹ የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ተዛምዶ ደረጃው ዝቅተኛ ሆኖ ተገኝቷል፡፡ በተጨማሪም ተማሪዎች ለማንበብ ያላቸው አመለካከትና የትምህርት ውጤታቸው ተዛምዶ እንዳለው ተጠንቶ ተዛምዶው ዝቅተኛ ደረጃ እንዳለው ተረጋግጧል፡፡ በጥናቱ በፆታ ምክንያት የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ ልዩነት እንዳለው ታውቋል፡፡ ለዚህም በጥናቱ  እንደ ምክንያት የተጠቀሱት ተማሪዎቹ የቀረበላቸውን ንባብ በግልፅና በትክክል አለመረዳታቸው፣ የንባቡን መዋቅር፣ ይዘትና ቴክስት ለመተቸት አለመቻላቸው ናቸው፡፡
ፒትስቸር (2010) በተመሳሳይ ባደረጉት ጥናት በተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የማንበብ ችሎታ ውጤት መካከል ያለውን ተዛምዶ ቃኝተዋል፡፡ በ32 ተማሪዎች ላይ በተደረገው ጥናት የተገኘው ውጤት እንደጠቆመው የተዛምዶው መጠን ዝቅተኛ ነው፡፡ በጥናቱ የመጀመሪያ ደረጃ ትምህርት ቤት ተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የማንበብ ውጤታማነት መካከለኛ ተዛምዶ ሲኖረው፣ በመካከለኛ ደረጃ ትምህርት ቤት የሚማሩት ዝቅተኛ ተዛምዶ አስመዝግበዋል፡፡    
ከዚህ ጥናት ጋር በተያያዘ ናንሲ (1989) ከ 1ኛ እስከ 8ኛ ክፍል የሚማሩ ተማሪዎችን ለማንበብ ያላቸውን አመለካከትና የማንብ ችሎታ ውጤት ተዛምዶ አጥንተዋል፡፡ በጥናቱ የተሳተፉ 876 ተማሪዎች ከሞሉት የማንበብ አመለካከት መለኪያ መጠይቅና የአንብቦ መረዳት ችሎታ ፈተና  የተገኘው ውጤት እንደሚያስረዳው (1) በተማሪዎቹ የማንበብ አመለካከትና የንባብ ውጤታማነት መካከል ተዛምዶው  ዝቅተኛ ሆኖ ተገኝቷል፤ (2) የማንብቦ ችሎታ ውጤታቸው ደረጃው መካከለኛ ሆኗል፤ (3) እስከ ስምንተኛ ክፍል ባሉት የትምህርት ደረጃዎች የማንበብ አመለካከታቸው ቀንሷል፤ (4) ከወንዶቹ ተማሪዎች በተሻለ የሴት ተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የንባብ ውጤታማነት ተዛምዶ ከፍተኛ ሆኗል፤ (5) የ7ኛ እና 8ኛ ክፍል ተማሪዎች የማንበብ አመለካከት አዎንታዊ እንደነበር ተጠቁሟል፤ (6) በሴትና በወንድ ታሪዎች መካከል የማንበብ ብቃትን በሚመለከት ጉልህ ልዩነት አልታየም፤ (7) ዝቅተኛ የማንበብ ችሎታ ውጤት (achievement) ያላቸው ተማሪዎች የማንበብ አመለካከታቸውም ቀንሷል::
በተጨማሪም ባስ (2012) የተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና የመፃፍ ዝንባሌ ተዛምዶ እንዳላቸውና እንደሌላቸው አጥንተዋል፡፡ ተመራማሪው በቱርክ ሐገር ኒጋዳ ትምህርት ቤት በ450 ተማሪዎች ላይ ባደረጉት ጥናት በመጠይቅ የተሰበሰበው መረጃ ውጤት እንዳመለከተው በማንበብ አመለካከትና በመፃፍ ዝንባሌ መካከል አዎንታዊ ተዛምዶ አለ ፡፡ እንዲሁም የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት የመፃፍ ዝንባሌያቸውን የመተንበይ ድርሻው የጎላ ነው፡፡
በተመሳሳይ ተራቪስ (2010) የተማሪዎች የማንበብ አመለካከትና ስነፅሁፍ የማንበብ ልምዳቸው ተዛምዶ መኖርና አለመኖሩን መርምረዋል፡፡ ለ18 ወራት በተደረገው ጥናት የተማሪዎቹ የማንበብ አመለካከት፣ የንባብ ልምድና በተጓዳኝም ሥነ ፅሁፍን የማንበብ ተነሳሽነታቸው በመጠይቅ መጠናዊና ዓይነታዊ መረጃ ተሰብስቦ የተገኘው ውጤት እንዳመለከተው ተማሪዎች የማንበብ አመለካከታቸው በጐለበተ መጠን ልምዳቸው በመዳበሩ የማንበብ ተነሳሽነታቸው ወደ ከፍተኛ ደረጃ ሊለወጥ ችሏል፡፡ በጥናቱ ተማሪዎች ለረጅም ጊዜ እያነበቡ የመቆየት ልምዳቸው በአመለካከታቸው ላይ ለውጥ አልታየበትም፡፡
ከዚህም ሌላ የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ በፆታ ልዩነት ተዛምዶ እንዳለውና እንደሌለው ለመመርመር የተደረጉ ጥናቶች አሉ፡፡ ዊዊ (2009) በቻይና ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤቶች የፆታ ልዩነት ከአንብቦ በመረዳት ችሎታ ጋር ያለውን ተዛምዶ መርምረዋል፡፡ በመጠይቅና በክለሳ ድርሳን ሪፖርት የተሰበሰቡት መረጃዎች እንዳመለከቱት ሴት ተማሪዎች ከወንድ ተማሪዎች በተሻለ ሁኔታ ብልሐቶችን በመጠቀም፣ የንባብ ጭንቀትን በመቋቋም እንዲሁም አንብቦ በመረዳት ችሎታ የተሻሉ ሆነው ተገኝተዋል፡፡
በተመሳሳይ ሮዊል (1972) የማንበብ አመለካከትን የሚለውጡ ምክንያቶችን ለመመርመር ጥናት አድርገዋል፡፡ በጥናታቸውም የማንበብ አመለካከት አንብቦ ከመረዳት ችሎታ፣ ቃላትን ከመለየት፣ ከፆታ፣ ከዕድሜና ከማሕበራዊ ደረጃ ጋር ያለውን ተዛምዶ አጥንተዋል፡፡ ተመራማሪው የጥናቱን ተሳታፊዎች በሙከራ ቡድንና በቁጥጥር ቡድን በመከፋፈል ከሰበሰቡት መረጃ የተገኘው ውጤት እንዳመለከተው የማንበብ አመለካከት በፆታ፣ በዕድሜና በማህበራዊ ደረጃ ተዛምዶው በስታስቲክስ ጉልህ ልዩነት አልተገኘበትም፡፡ ልዩነት የታየው ቃላትን ተገንዝቦ በመለየት ላይ ነው፡፡
በጥናቶቹ እንደተጠቆመው የማንበብ አመለካከትና የአንብቦ መረዳት ችሎታ እንዳይጎለብት የሚያደርጉት ምክንያቶች አዎንታዊ የማንበብ አመለካከት እንዲዳብር ትኩረት ባለመሰጠቱ፣ መምህራን የበርካታ ተማሪዎቻቸውን የማንበብ አመለካከት ዝንባሌ ግምት ውስጥ ሳያስገቡ የዕለት ተዕለት ተግባራቸውን ማከናዎናቸው እንዲሁም ወላጆች ማንበብን የትርፍ ጊዜ ተግባር አድርገው መቁጠራቸው ናቸው (ሮዊል 1972፣ ዊዊ 2009)፡፡                    
ከዚህ በተለየ አቡ-ራቢያ (1996) አመለካከቶችና ባሕላዊ ዳራ በሁለተኛ ቋንቋ አንብቦ ከመረዳት ችሎታ ጋር ያላቸውን ተዛምዶ ከሶስት ማሕበራዊ አውዶች ጋር በማነፃፀር ጥናት አድርገዋል፡፡ በጥናቱ ከተሳተፉት እስራኤላዊ አረብ፣ እስራኤላዊ አይሁድና ካናዳዊ አረብ ተማሪዎች የተገኘው ውጤት እንደሚያስረዳው በራሳቸው ባሕል የቀረበላቸውን ፅሁፍ የተፈተኑ የጥናቱ ተሳታፊዎች የማንበብ አመለካከትና ፍላጎታቸው እንዲሁም አንብቦ የመረዳት ችሎታቸው የተሻለ ሆኖ ተገኝተል፡፡ የካናዳዊ አረቦቹ ቡድን ውጤት ከእስራኤል አረቦቹና ከአይሁድ አረቦቹ ጋር ሲነፃፀር የቴክስቱ ይዘት ሳይሆን የቴክስቱ ቋንቋ አንብቦ ለመረዳት ተፅዕኖ አሳድሮባቸዋል፡፡
በተጨማሪም ግሪአኒ (1987) የማንበብ አመለካከት፣ የመኖሪያ አካባቢና የማንበብ ፍላጎት ከማንበቢያ ትርፍ ጊዜ (leisure-time reading) ጋር ያላቸውን ተዛምዶ በሚመለከት በጥናታቸው ቃኝተዋል፡፡ ከጥናቱ የተገኘው ውጤት እንደሚያስረዳው የመኖሪያ አካባቢና የማንበቢያ ትርፍ ጊዜ ተዛምዶ አላቸው፡፡ ከሌሎቹ ተለዋዋጮች በላቀ ሁኔታ የማንበብ አመለካከት ከማንበቢያ ትርፍ ጊዜ ጋር በጥብቅ ይዛመዳል፡፡ የማንበብ ፍላጎትና የማንበቢያ ትርፍ ጊዜ ያላቸውን ተዛምዶ በሚመለከት ጥናቱ እንዳመለከተው ለመዝናኛ ንባብ ካልሆነ በስተቀር ትርፍ የማንበቢያ ጊዜ ለትምህርታዊ ንባብ ብዙም ጥቅም ላይ አልዋለም፡፡
ቡክሆረስት-ሄንግና ፔሪራ (2008) በአንድ የሲንጋፖር ሁለተኛ ደረጃ ትምህርት ቤት በዓመቱ የትምህርት ማብቂያ ተማሪዎች አሉታዊ የማንበብ አመለካከት ሊያድርባቸው የቻለበትን ምክንያት አጥንተዋል፡፡ ለዚህም ትርፍ ጊዜን በንባብ ተግባር ላይ አለማዋል በማንበብ አመለካከት ላይ ተፅዕኖ ማሳደሩ ታውቋል፡፡ በጥናቱ የተገኘው ውጤት እንዳመለከተው በማንበብ አመለካከት በሴቶችና በወንድ ተማሪዎች መካከል የጎላ ልዩነት አልታየም፤ ሁሉም የጥናቱ ተሳታፊዎች የማንበብ ውስጣዊ ፍላጎታቸው ግን በከፍተኛ ሁኔታ ቀንሷል፡፡
በአጠቃላይ ከጥናቶቹ ውጤት ለመረዳት እንደሚቻለው የማንበብ አመለካከትና አንብቦ የመረዳት ችሎታ ተዛምዶ አላቸው የሚሉ ተመራማሪዎች አሉ ለምሳሌ ሳላበስ (2008)፣ አቡ-ራቢያ (1996)ን መጥቀስ ይቻላል፡፡ በሌላም በኩል ተዛምዶው ቢኖርም በዝቅተኛ ደረጃ ላይ እንደሚገኝ የጠቆሙ ተመራማሪዎች አሉ (ግሪአኒ 1987፣ ቡክሆረስት-ሄንግና ፔሪራ 2008)ን መጥቀስ ይቻላል፡፡
 2.3. የማንበብ አመለካከት አንብቦ ለመረዳት ያለው ሚና
ወላጆች የማንበብ አመለካከትን ለማሳደግና ለማጠናከር በመኖሪያ ቤት ውስጥ  ሁለት ሚናዎችን  ይጫወታሉ፡፡ የመጀመሪያው ሚና ማንበብን ባህላቸው አድርገው የሚነበቡ ነገሮችን በመኖሪያ ቤት ውስጥ ማስቀመጣቸው ሲሆን፣ ሁለተኛው ሚና በማንበብ ልምዳቸው አማካኝነት  ለልጆቻቸው አዝናኝና አስተማሪ ድርሳናትን እያነበቡላቸው ተፅዕኖ ማሳደራቸው ናቸው፡፡ ወላጆች የማንበብ ልምዳቸውን በማዳበር ለልጆቻቸውም አርአያ ከሆኑ ልጆቻቸው በመኖሪያ ቤት ውስጥ እንዲያነቡ ምቹ ሁኔታ ይፈጥራሉ (ስፓይገል 1994)፡፡ ወላጆችና የመኖሪያ ቤት አካባቢ በአመለካከት ላይ የሚያሳድሩት ተፅዕኖ በጎ ከሆነ በትምህርት ቤት አወንታዊ አመለካከትን ለማጠናከር ለሚደረገው ጥረት በቅርበት አብሮ ለመስራት ያግዛቸዋል (አሌክሳንደርና ፊለር 1976)፡፡
በተጨማሪም ስችማይት (2009) የተማሪዎችን አወንታዊ የማንበብ አመለካከቶች ማሳደጊያና ማጠናከሪያ ናቸው በማለት የሚዘርዝሯቸው 5 መንገዶች አሉ፡፡ እነሱም በመኖሪያ ቤት ውስጥ የሚገኙ ወላጆች፣ በትምህርት ቤት አካባቢ ያሉ የመማሪያ ክፍሎች፣ በተለያዩ መሳሪያዎች የሚሰበሰቡ የአመለካከት ግምገማዎች፣ የማስተማር ልምዶች፣ የተማሪዎችና የመምህራን አመለካከትና ባህሪያት ናቸው፡፡
ይህንን ሀሳብ በመቃረን ክራመር (1994)፣ ዊየርና ዊየር (1994)ና ብሮፊ (2004) የማንበብ አመለካከትን ለማሳደግና ለማጠናከር የሚቻለው በመኖሪያ ቤት ሳይሆን በመማሪያ ክፍል ውስጥ ብቻ ነው በማለት ይከራከራሉ፡፡ ለዚህ አባባላቸው በምክንያትነት የሚጠቅሱት የመምህራንና የተማሪዎች የመማሪያ ክፍል ውስጥ ተራክቦ፣ ንቁ የሆነ የመማር መነሳሳት ካለ፣ የመማሪያ መፃሕፍት  በተማሪዎች ፍላጎት መሰረት ከተመረጡ፣ መምህራን በተማሪዎች የመማሪያ ክፍል ውስጥ ቤተ- መፃህፍት ካዘጋጁ በመማሪያ ክፍል ውስጥ ብቻ የማንበብ አመለካከትን ማሳደግና ማጠናከር ይቻላል፡፡
በዚህ ሀሳብ የማይስማሙት ማክኪና፣ ኪአርና ኢልስዋርዝ (1995) የመምህራንና የተማሪዎችን አመለካከቶችና ባህሪያት ጠንቅቆ በማወቅ የማንበብ አመለካከትን ማሳደግና ማጠናከር ይቻላል ይላሉ፡፡ በተጨማሪም ተማሪዎች ለማንበብ ያላቸውን አዎንታዊና አሉታዊ ምክንያት በመገንዘብ ለችግሮቹ መፍትሔ ፈልጎ ያላቸውን ማጠናከር፣ የሌላቸውን መፍጠር ይቻላል፡፡ ልጆች በመኖሪያ ቤትም ሆነ በትምህርት ቤት በትርፍ ጊዜያቸው እንዲያነቡ ሁኔታዎች ከተመቻቹላቸው፣ ወላጆችና መምህራን ደካማና ጎበዝ እያሉ በአንባቢያን መካከል ልዩነት ካልፈጠሩ፣ መምህራን በትምህርት ቤት ውስጥ  ጎበዝ ተማሪዎች የማንበብ አመለካከታቸው አዎንታዊ ሲሆን፣ የሰነፍ ተማሪዎች ግን አሉታዊ ነው በማለት ተማሪዎችን ካልከፋፈሉ፤ በፃታ ፣በዕድሜና በጎሳ አማካኝነት የማንበብ  ተፅዕኖን አጥንቶ መፍትሔ ከተፈለገ የማንበብ አመለካከትን የትም ቢሆን ማሳደግና ማጠናከር ይቻላል፡፡
ከዚህ በተጨማሪ ራሲኒስኪና ፓዳክ (2000) እንዳመለከቱት የተማሪዎች ንባብ ስኬታማ እንዲሆን መምህራን መፃሕፍትን ማንበብ በመውደድ አርዓያ ሊሆኗቸው ይገባል፡፡ መምህራኑ ለተማሪዎቻቸው የማንበብ አርአያ ከሆኑ፣ በመማሪያ ክፍል ውስጥ የማንበብ ፍላጎትን ለማነሳሳት ተቀባይነት ያገኛሉ፡፡ አርአያ በሚሆኑበት ወቅት ከመምህራኑ የሚጠበቀው ክንውን ተማሪዎቻቸው በዝምታ ንባብን ሲያነቡ እንዲመለከቷቸው ማድረግ ሳይሆን፣ ካነበቡት ምንጭ እየጠቀሱ ማንበብ ሕይወታቸውን እንዴት እንደለወጠው ለተማሪዎቻቸው ቢነግሯቸው ተማሪዎችም ከማንበብ የሚገኘውን ጥቅም በመረዳት አንባቢ የመሆን አመለካከታቸው ሊያድግና ሊጠናከር ይችላል፡፡ ጋምብሪል (1996) እንዲሚገልፁት፣ ተማሪዎቻቸው ፈላስፋ፣ ተማራማሪ፣ ደራሲና ሐያሲ እንደሚሆኑላቸው የሚመኙ መምህራን እነሱም ተፈላሳፊ፣ ተመራማሪ፣ ተባባሪ፣ አንባቢ፣ ፀሐፊና ገምጋሚ መሆን አለባቸው፡፡
በተመሳሳይ ራስኒስኪና ፓዳክ (2000) እንዳመለከቱት ተማሪዎች ለማንበብ ያላቸው አመለካከት አዎንታዊ እንዲሆን የሚፈልጉ መምህራን እነዚህን አራት ጠቃሚ ዕምነቶች አዋህደው መያዝ ይጠበቅባቸዋል፡፡ እነሱም(1) ሁሉም ተማሪዎቻቸው ለመማር እንደሚፈልጉ ተስፋ ማድረግ፤(2) ተማሪዎች ወደ መማሪያ ክፍል ይዘዋቸው የሚመጡትን ከማንበብ ጋር የተያያዙ ነገሮች ትኩረት መስጠት፤(3) ተማሪዎች በንባብ ትምህርት ተግባራት ከማይተገብሩት ይልቅ የሚተገብሩትን ተግባር በትኩረት መቃኘት፤(4) በተማሪዎች ፍላጎትና ጠቀሜታ ላይ ተመስርቶ የተቃኘ ማስተማር፣ መማርን ቀላል  እንደሚያደርገው ማመን ናቸው፡፡
በአጠቃላይ በምርምሮቹ እንደተገለፀው የማንበብ አመለካከት ለተማሪዎች የማንበብ አመለካከት ሚናው የጎላ ነው፡፡ መምህራንና ወላጆች አዘውትረው ለማንበብ ያላቸው አመለካከት አሉታዊ ከሆነ ተማሪዎችም ለማንበብ ያላቸው አመለካከት እየቀነሰ ይሄዳል፡፡ ስለዚህም የተማሪዎች የማንበብ አመለካከት እንዲያድግና እንዲጠናከር የተማሪዎች፣ የወላጆችና የመምህራን አመለካከት አዎንታዊ መሆን አለበት፡፡